ከመቀሌ ጉዞዬ በጣም በጥቂቱ


ከመቀሌ ጉዞዬ በጣም በጥቂቱ
በአርቲሎ ገልገሎ
የአለፉት ቀናት እጅግ አሰልቺ ነበሩ። እንደኔ ከፍታ ቦታ ላይ "ፎቢያ" ላለበት ሰው የሁለት ቀን ጉዞን በተንቀረፈፈ መኪና መጓዝ ማለት እስር ቤት የመከተት ያህል ይከብዳል። በዚህም ምክንትያት ምንም እንኳ ወደ ሰሜን ለመሄድ ባልፈልግም በአለቃዬ ግፊት ጉዞዬን ለማድረግ ቅዳሜ ከሌሊቱ አስር ሰአት ላይ ከመኪናው ራዲያተር እኩል ስሜቱ ቶሎ ከሚፈላው የድርጅታችን ሹፌር ጋር ጉዞ ወደ ሰሜን ተጀመረ።
አዲስ አበባን ለቅቄ መቀሌ እስክደርስ ያሉት ተራሮች ፈጣሪ ሌላ አለም ላይ ማስቀመጫ ቦታ አጥቶ እዚያ ያስቀመጣቸው እንዲመስለኝ ነው ያደረገኝ። የትግራይ ክልል ተራሮች እስከእለተ ሞታቸው ላለመፋታት ቃል የተገባቡና አንድ ላይ የተሰባሰቡ ፍቅረኛሞችን ነው የሚመስሉት። የሰሜን ተራሮች አንገት ለአንገት ተቃቅፈው ላያቸው " ተራሮችም ስለፍቅር ግንዛቤ አላቸውእንዴ?” ያስብላል።

የሚገርመው ግን ምን ተራራዎቹ ለእይታ ቢከብዱም የሰሜኑ ሰው ዝም ብሎ አላያቸውም። ከደርግ ጋር በተደረጉ ጦርነቶች ምሽጉ፣ ከትጥቅ ትግሉ ኋላ በነበሩት አመታት ደግሞ ተራራውን አርሶ ድንጋዩን አለስልሶ የእለት ጉርሱን ማብሰያ አድርጓቸዋል። በአረንጓዴ ልማቱም ተራራን በማልማት ሂደቱ ውስጥ የትግራይ ህዝብ ለአለም አቀፍ ማህበረሰብ ተምሳሌት መሆን ችልዋል::

መቀሌን ለማግኘት በሚደረጉ ጉዞዎች አንድ መኪና ጥምዝምዝ የሰሜን ተራራዎችን መጓዝ ግድ ይለዋል። እንደ አላማጣ ያሉ "ለማጣ" መንገዶች ለተራራ አድናቂ የልብ ትርታው ከፍ የሚልበት፣ ለዝቅተኛ ስፍራ አድናቂ ደግሞ ካሁን አሁን ተራራው አለቀ ብሎ ከእራሱ ጋር አኩኩሉ የሚጫወትበት ትእይንትን ይፈጥራል።

የትግራይ ተራሮች ይህ ብቻ አይደለም ታሪካቸው። ፋሺስታዊው የደርግ አየር ድብባም ሌላው ታሪካቸው ነው። ለጻነት በተደረጉ እልህ አስጨራሽ ትግሎች የነአላማጣና የነኮረም እንዲሁም ሌሎች ተራሮች የሰማእታትን ደም ጠጥተዋል። እናት ህጻንዋን አጥግባ ሳታጠባ ለፋሺስታዊ ቦምብ መስዋእት ሆናለች።

በመቀሌ የተገኘሁት ህወሃት የትጥቅ ትግሉን የጀመረበትን 40 አመት ለማክበር ነበር። መቀሌ ተውባና ተኳኩላ ነበር የጠበቀችኝ። የትግራይ ህዝብ ዘውዳዊውና ፋሺስታዊው ስርአት ከደረሱበት ቁስል ተላቆ ኑሮውን ለማሸነፍ ደፋ ቀና ማለት ከጀመረ ከሁለት አስር አመታት በላይ አስቆጥርዋል። መቀሌ የሚገባትን ያህል አድጋለች ብሎ መናገር ቢከብድም ያለፉት ስርአቶች ያሳደሩባትን ጠባሳ እረስታ አሁን ወደ ልማት የምታደርገው ጉዞ ተስፋ እንዳላት አመላካች ነው። በከተማዋ ያሉ አዳዳዲስ ኢንደስትሪዎች ደግሞ ለዚህ አይነተኛ ምሳሌ ናቸው።

የመቀሌ ህዝብ የህወሃትን በአል ለማክበር የካቲት 11 አልጠበቀም። በከተማዋ ከእለቱ ቀደም ብለው በነበሩ ሲምፖዚየሞችና የዋዜማው ቀን የጎዳና ትእይንት ላይ ንቁ ተሳትፎ ሲያደርግ አስተውያለሁ። ህጻናት፣ አዛውንት፣ ወጣቱ፣ ሴቱ፣ ቄሱ መምህሩና፣ ተማሪው በነቂስ ወጥቶ የድል በአሉን ሲያጣጥም አስተውያለሁ። በተለይም ደግሞ በዋዜማው የነበረው የከተማዋ ውበት ልብ ይነካል። የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ፎቶን የለጠፉ ባጃጆችና ተሽከርካሪዎችን መመልከት ከከተማዋ ትእይንቶች አንዱ ነበር። በእለቱ የመቀሌና ያጎራባች አካባቢ ህዝብ የክልሉን ባንዲራ በተለያዩ መንገዶች ለብሶ ይስተዋል ነበር።

የካቲት 10 እጅግ ውብ ምሽትን ነው ያስተናገደው። የመቀሌ ህዝብ እንግዶቹን እያስተናገደ እሱም ሲፈነድቅ ነው ያመሸው። እንደ ድሮ ቢሆን ኖሮ ይህ ህዝብ ምናልባትም ከሰማይ የሚወነጨፍበትንፋሺስታዊ የደርግ አዎርፕላኖች ሊወነጨፉበት የሚችሉትን ሚሳኤሎች ሊያመልጥ የሚችልበትን መንገድ ነበር የሚያመቻቸው። ዛሬ ግን የትግራይ ህዝብ የመከላከያ አየር ሃይል ጀቶች ትእይንት ሲያሳዩ በፍቅር ነው የሚመለከታቸው።የጀቶቹ አክሮባቲክ የሆ እንቅስቃሴ ክብርን እንጂ ሞትን ይዞ አይደለም የመጣው።
የካቲት 10 የመቀሌ ሰማይ እራሱ ለየት ያለ ትውስታ እንደሚኖረ ጥርጥር የለኝም። ምክንያቱም የሚበሩት ጄቶች ቦምብ ለማውረድ ሳይሆን ሉአላዊነተን ለማውራት ስለሆነ። የመቀሌ ሰማይ ሌሊቱን በርችት ሲደምቅ ነው ያመሸው::

በመቀሌ የነበረኝ ቆይታ እጅግ አጭር ስለነበር ስለ መቀሌ ህዝቦች ብዙ ማውራት አለችልም። ግን ያየሁትን ከመናገር ወደኋላ ማለት አልፈልግም። እዚህ አዲስ አበባ ሳለሁ ጆሮዬ የሰማውና በመረጃ ያልተደገፈው አመለካከቴ ላይ አፍሬያለሁ። ምክንያቱም የትግራይ ህዝብ በተለይም የመቀሌ ነዋሪ ከሌላው የማህበረሰብ ክፍል ከመንግስት ልዩ የኢኮኖሚ ድጋፍ እንደሚደረግለት፣ ከተማዋም ትልቋ "ቦሌ" የሃብታሞች ብቻ መኖሪያ አድርጌ ነበር የገመትኳት። በእርግጥ ተሳስቻለሁ። በመቀሌ ሁሉም አይነት የህብረተሰብ ክፍል አለ። ሃውም፣ ሃብታሙም ለማኙም፣ ክርስቲያኑ፣ ሙስሊሙ፣ እብዱ ፣ሴተኛ አዳሪው..... ሁሉም እንደሌላው የሃገሬ ህዝብ ናቸው።

በትግራይ ጉዞዬ የተለያየ አይነት ባህሪ ያላቸውን ሰውችንም ለማየት ችያለሁ። ካላቸው ቀንሰው ለማስተናገድ ወድኋላ የማይሉትን የአላማጣና የኮረም ትግሬዎችን አይቻለሁ።

በመቀሌ ቆይታዬ ሌላው የገረመኝ ነገር እነ ዶክተር አርከበን በመሃል የመቀሌ ጎዳናዎች በነጻነት ሲራመዱ ማየቴ ነው። መንገድ ላይ የሚያገኙትን ሰው እንደወንድም እያቀፉ ሲስሙ ሳይ ቅናት ቢጤ ተሰምቶኛል። ምክንያቱም እዚህ አዲስ አበባ እንኳን እነ ዶክተር አርከበን የአንድ ሚኒስቴር ምስሪያ ቤት ዳይሬክተርን በቅርብ እርቀት ለመመልከት ድፍረት ወይም እድል ያስፈልጋል።

በሃገረ ሰላም (አዲገዛኢ) የነበረኝ ቆይታ ሌላው አስደሳች የትግራይ ትውስታዬ ነው። ይህ ስፍራ በተራራ ዋሻ ውስጥ የተደበቁ ድንቅ ቢሮዎችን ይዟል። ቦታው የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትርና የትግል አጋሮቻቸው 1980ዎቹ ለነበረው እልክ አስጨራሽ የትጥቅ ትግል የፕሮፓጋንዳና ሌሎች እንቅስቃሴዎች በቢሮነት ሲያገለግል ነበር። በእያንዳንዱ ቢሮ ውስጥ ውስጥ አንዲት እጅግ አነስተኛ አልጋ፣ አንድ ጠረጴዛ፣ ፋይል ማስቀመጫ፣ የመጽሃፍ መደርደርያ፣ካርታዎች እና የመሳሰሉትን ይዟል። ስፍራው ሃይማኖታዊ ባይሆንም የገዳምነት ባህሪ አለው። ለአዲሲትዋ ኢቲዮጵያ ትልቅ የፖለቲካ ገዳም።

Comments

Popular Posts